Wednesday, January 17, 2018

“ከሐሰተኞች ነቢያት ተጠንቀቁ ፡፡” ማቴ.7፤16 ክፍል ሰላሳ ሰባት

ከክፍል ሰላሳ ስድስት የቀጠለ፦

የተወደዳችሁ አንባብያን! እንኳን ለጌታችን ለመድኃኒታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ የልደቱና የጥምቀቱ መታሰቢያ በዓላት በሰላምና በጤና አደረሳችሁ አደረሰን፡፡
     ሁላችንም የኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ሃይማኖት ተከታዮች እንደምናውቀው፤ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሰማየ ሰማያት ወርዶ፤ ንጽሕት ቅድስት ከምትሆን ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም ተወልዶ፤በዚህ ዓለም በቆየባቸው ሰላሳ ሶስት ዘመናት ማለትም በመዋዕለ ሥጋዌው የፈጸማቸው ሥራዎች በሁለት ዐበይት ክፍሎች ይከፈላሉ፡፡አንዱና ዋነኛው አዳምና ልጆቹ የተያዙበትን የበደል ዕዳ ዋጋ ከፍሎ /ቤዛ ሆኖ/ ነጻ ለማውጣት ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ ለአብነት /ለአርአያነት/ ነው፡፡በቤዛነት ሥራው የሰው ልጅ ሊሳተፍበት ስለማይችል እሱ ብቻ የፈጸማቸው ናቸው፡፡ከነዚህ ውስጥ ከእመቤታችን በድንግልና መወለዱ፣ በዮርዳኖስ ወንዝ ሲጠመቅ በዚያ ተቀብሮ የነበረውን የዕዳ ደብዳቤያችንን መደምሰሱ፣ በመጨረሻም በጽንስ የጀመረውን የቤዛነት ሥራ በመስቀል ላይ በመፈጸም የከፈለው ካሳ የሚጠቀሱት ናቸው፡፡በሌላ በኩል እሱ ጾሞ እንድንጾም፣እሱ ጸልዮ እንድንጸልይ፣እሱ ሰግዶ እንድንሰግድ፣ እሱ ለችግረኞችና ለበሽተኞች እንደ አዘነላቸውና እንደረዳቸው እኛም እንዲሁ እንድናደርግ፤ በአጠቃላይ ተከተሉኝ ባለን መንገድ ሁሉ እንድንከተለው፤በአምላካዊ ቃሉ እንዲህ ሲል አስተምሮናል፤"….ብትወዱኝ ትእዛዜን ጠብቁ…..! /ዮሐ.14፥15/ "....እርስ በርሳችሁ ትዋደዱ ዘንድ ትእዛዜ ይህች ናት…..."!  / ዮሐ.15፥12/፡፡አኛም የእግዚአብሔር የጸጋ ልጆች እስከሆንን ድረስ ትእዛዙን መፈጸም ይገባናል፡፡
     የተወደዳችሁ አንባብያን! የጌታችንን የልደቱን መታሰቢያ በዓል ታሕሳስ ሃያ ዘጠኝ ቀን አክብረን የጥምቀቱን በዓል ለማክበር እየተዘጋጀን ባለንበት ሰዓት፤ሁለቱንም በዓላት በማስመልከት ከማሕበራዊ ድረ-ገጽ ያገኘነውንና ለብዙዎቻችን ጥያቄ መልስ የሚሰጡንን ትምህርቶች ልናካፍላችሁ ወደድን፡፡ልደቱን በተመለከተ "Ydidya Mesgana"የተባሉ፤ ጥምቀቱን በተመለከተ ደግሞ "ሊቀ ጉባኤ ጌታሁን ደምፀ" የተባሉት መምህር የሰጡትን ትምህርት፤ ጸሁፉን ለንባብ እንዲመች ከማስተካከል በስተቀር በሃሳቡ ላይ ምንም ሳንጨምርና ሳንቀንስ አቅርበንላችኋል፡፡

መልካም ንባብ! መልካም በዓል!