Sunday, March 27, 2016

“ከሐሰተኞች ነቢያት ተጠንቀቁ ፡፡” ማቴ.7፤15 ክፍል አስራ ስድስት

ከክፍል አስራ አምስት የቀጠለ
የተከበራቸሁ አንባብያን!
በዚህ የመወያያ መድረክ (ወልድ ዋሕድ) ክፍል ስድስትና ሰባት ቤተ ክርስቲያናችን በመዝሙር በኩል እየገጠማት ያለውን ፈተና በማስመልከት ባቀረብነው ጽሁፍ መጠነኛ ግንዛቤ እንዳገኛችሁ እናምናለን፡፡ከዚህ በመቀጠል ደግሞ "Bini Zelideta" ከተባሉ ወንድማችን ከፌስ ቡክ ገጻቸው ላይ ያገኘነውን ጽሁፍ አስተማሪ ሆኖ ስላገኘነው እንድታነቡት እንጋብዛለን፡፡
መልካም ንባብ!
Bini Zelideta
የተሃድሶ መናፍቃን መዝሙራት ሥውር ተልዕኮ!”
ክፍል-1 (ስለ ነገረ ክርስቶስ) /መልዕክቱ የረዘመው ግጥሞች ስለበዙበት ነው/
መግቢያ
ቅድስት፤ኦርቶዶክሳዊት ሃይማኖታችን ዕረፍት አልባ ዘመናትን ስታሳልፍ ዛሬ 2008 ዓመቷ ነው፡፡ ፈተናዎቿም እንደየ አዝማናቱና እንደፈታኞቿ የተለያዩ ነበሩ፡፡ ሠይፍ፣የዐላውያን መከራ፣የአናብሥት ትግል፣የክርስቲያኖች ስቃይ የሮም ኮሎሲየም አምፊ ቴአትር ትርዒት፣የቁም እሳት ቃጠሎ፣የካታኮምቡ ሕይወት፣የሠንሠለት ኑሮ እና የመንኩራኩር ስቃይ የመጀመሪያው እልህ አስጨራሽ ፈተናዋ ሲሆን እግር ተከትሎ፤ዓይነቱን ቀይሮ የመጣው የአርዮሳውያን ሃይማኖትን የመቀየር፣አስተምሕሮዋን የመበረዝ እንቅስቃሴ ጣሯን፣ሰቀቀኗን፣መከራዋን አብዝቶባት ቆይቷል፡፡ ዮዲት ጉዲት፣የካቶሊክ ሚሲዮናውያን፣ጽንፈኛ አሕዛቦችና የሉተር ርዝራዦች ዞረው ዞረው ሲሻቸው አንድ ላይ ሲሻቸው ደግሞ በፍርርቅ በመከረኛይቱ ሃይማኖት ላይ ቀንበር ሲጭኑ ኖረዋል ዛሬም ዕረፍት የላትም! የገሃነም ደጆች አይችሉአትም ተብሎ ስለተጻፈው አማናዊ ቃል ሁሉን አልፋ ዛሬ ብትደርስ ለሆዳቸው ያደሩ ሥጋውያን አስተምህሮዋን እናድሳለን ብለው ተነሡባት፡፡ ይህ ከቀደምት ዘመናት በዓይነትም በቅርጽም አካሄዱን ቀይሮ ቤተ ክርስቲያንን የማዳከም ሥልት ይዞ የተነሣው ፕሮቴስታንታዊ ቡድን ስውር ተልዕኮውን በቅድስት ቤተክርስቲያን ላይ በመሰንዘር ከፍተኛ ጥፋት አድርሷል አሁንም በማድረስ ላይ ይገኛል፡፡ የሃይማኖት ቅብ ይዘው፣ተቆርቋሪ መስለው መንገዷን ስታለች፣አስተምህሮዋ ልክ አይደለም፣አርጅታለች፣እናድሳታለን ባዮች ሲሆኑ በትምርቶቻቸው እና ከዘፈን በተቃኙ መዝሙሮቻቸው ትውልድን መበረዝ የዕለት እንጀራቸው አድርገውታል፡፡ በተለይም መዝሙሮቻቸው በአንድ ሌሊት ተደርሰው ንጋቱን ለጆሮ ስለሚበቁ ኑፋቄን ለማሰራጨት ደገኛ መሣሪያቸው ሆኖ በማገልገል ላይ ይገኛል፡፡

“ከሐሰተኞች ነቢያት ተጠንቀቁ ፡፡” ማቴ.7፤15 ክፍል አስራ አምስት

ከክፍል አስራ አራት የቀጠለ
"እያወቁ ማለቅ"
"ያላወቁ አለቁ ነበረ ተረቱ፤
እያወቁ ማለቅ መጣ በሰዓቱ፡፡"
     በሰማይም ሆነ በምድር ላይ ሁሉን ቻይ ከሆነው ከልዑል እግዚአብሔር እውቅና እና ፈቃድ ውጪ የሚከናወን ምንም ነገር እንደሌለ ይታወቃል፡፡ይታመናልም፡፡ይሁን እንጂ  ለስሙ ክብር ምስጋና ይግባውና አምላካችን እግዚአብሔር ሰውን ከሌሎች ፍጡራን ለይቶ በመልኩና በምሳሌው ሲፈጠረው የማሰብ፣የመናገርና ሕያው ሆኖ የመኖር ዕድል ሰጥቶታል፡፡የሰው ልጅ በዚህ በተሰጠው አእምሮ መመራት አቅቶት በኃጢአት ቢወድቅ፤ይህንን አድርግ ይህንን አታድርግ የሚል የተጻፈ ህግ /ህገ ኦሪትን/ ሰጠው፡፡በዚህ ብቻ አላበቃም፤እራሱ እግዚአብሔር ወልድ ወደዚች ምድር መጥቶ ለሰው ልጅ የቤዛነቱንና የአርአያነት ሥራውን ፈጸሞለታል፡፡ ጌታችን መድሐኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ በጽንስ ጀምሮ በመሰቀል የፈጸመውን የቤዛነቱን ሥራ እፁብ! ድንቅ! ብሎ ከማመስገን በስተቀር በዚች አጭር ጽሁፍ የምንለው ነገር አይኖረንም፡፡በአርአያነት/በምሳሌነት/ ሥራው ግን ከኃጢአት በስተቀር የሰውን ህግ ሁሉ ፈጽሞ እኛም እንድንከተለው አዝዞናል፡፡በእኔ ያመነ እኔ የምሰራውን ሁሉ ያደርጋል፤እንደውም የበለጠ ያደርጋል ብሎ፡፡ዮሐ.14፥12፡፡

Sunday, March 6, 2016

“ከሐሰተኞች ነቢያት ተጠንቀቁ ፡፡” ማቴ.7፤15 ክፍል አስራ አራት

የተወደዳችሁ አንባብያን!
እንደምን ሰነበታችሁ ?
‹‹ከሐሰተኞች ነቢያት ተጠንቀቁ›› በሚለው ዐቢይ ርዕስ ሥር፤ በክፍል አስራ አንድና አስራ ሁለት ላይ ወቅታዊ የሆነውን የኢ/ኦ/ተ/ቤተ ክርስቲያን  የውስጥና የውጪ መናፍቃን/ተሐድሶዎች/ ችግር በማስመልከት ማህበረ ቅዱሳን በድረ-ገጹ (www.eotcmk.org) ያቀረበውን ዘገባ ተመልክታችሁ ጥሩ ግንዛቤ እንዳገኛችሁ በመገመት፤በመቀጠል ደግሞ "አምልኮተ ሰይጣን - ፍጻሜ “ተሐድሶ”?"
በሚለው ርዕስ ከማህበረ ቅዱሳን ድረ-ገጽ ያገኘነውን በማስረጃ የተደገፈ ዘገባ እነሆ ብለናል፡፡

መልካም ንባብ!