Friday, April 10, 2015

“ከሐሰተኞች ነቢያት ተጠንቀቁ ፡፡” ማቴ.7፤15 ክፍል ስድስት

እንኳን ለጌታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ የትንሣዔ በዓል በሰላም አደረሳችሁ!!!
በመዝሙር ስም ዘፈን! እስከ መቼ?

የተከበራችሁ የዚህ ድረ ገጽ ታዳሚዎች እንደምን ሰነበታችሁ?

     ባለፈው ክፍል አምስት ጽሁፋችን ‹‹በቀጣይ ሌላውን የክህደት መጽሐፋቸውን እንመለከታለን›› ብለን በይደር እንዳቆየነው ይታወሳል፡፡ ሆኖም ወደ ሌላው  መጽሐፋቸው ከመሄዳችን በፊት ቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያናቸንን በእጅጉ እየተፈታተናት ስላለው የመዝሙር ሁኔታ ጥቂት ግንዛቤ ለማስጨበጥ ቅድሚያ ሰጥተናል፡፡  
    ሁላችንም እንደምናውቀው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ / በጻድቁ በቅዱስ ያሬድ አማካይነት ከፈጣሪዋ ከልዑል እግዚአብሔር ልዩ የሆነ የዜማ ጸጋ ተሰጥቷታል፡፡ ስለሆነም ኢትዮጵያዊው አባታችን ቅዱስ ያሬድ ከቅዱሳን መላእክት የተሰጠውን ሰማያዊ ዜማ ተቀብላ መላውን አገልግሎቷን ትፈጽማለች ፡፡
     ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን እምነቷንና ሥርዓቷን ከአባቶች ወደ ልጆች ለማስተላለፍ እንዲሁ በልማድ ብቻ መቀጠሉ በቂ ስላልሆነ 1960ዎቹ አመታት ወዲህ ወጣቶችና ህጻናት በዕለተ ሰንበት በየአጥቢያ ቤተ ክርስቲያናቸው እየተሰበሰቡ ስለ ሃይማኖታቸው እንዲማሩ ‹‹መንፈሳውያን ማሕበራት›› ተቋቋሙ /ቤተ ክርስቲያናችን የምትመራበትን ቃለ ዓዋዲ 1970 እትም ይመልከቱ/፡፡ የእነዚህ መንፈሳውያን ማሕበራት ስያሜ ከጊዜ በኋላ ‹‹ሰንበት ትምህርት ቤት›› በሚለው  ተተክቶ እስከ አሁን እንጠቀምበታለን ፡፡ ከመንፈሳዊ ትምህርቱ ጎን ለጎን ግጥምና ዜማቸው በቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት የተዘጋጁ የአማርኛና የግዕዝ መዝሙሮችንና እንዲሁም በዓመቱ ውስጥ ለሚከበሩት ዐበይት በዓላት ተስማሚ የሆኑትን  መዝሙራት (ወረቦች) እንዲያጠኑ በማድረግ ወጣቱ ከያሬዳዊ ዜማ ሳይወጣ እውቀቱ በሚፈቅድለት መጠን ፈጣሪውን እንዲያመሰግንበትና እንዲማርበት ሲደረግ ቆይቷል፡፡እንዲሁም ከዚህም በተጨማሪ ከተወሰኑ ዓመታት ወዲህ ደግሞ ቤተ ክርስቲያናችን የሰርክ ጉባኤያትን በማዘጋጀት ለምዕመናን ከምታቀርበው የወንጌል ትምህርት ጎን ለጎን በነዚሁ መዝሙራት ፈጣሪያቸውን እንዲያመሰግኑ እያደረገች ነው፡፡

Saturday, February 21, 2015

“ከሐሰተኞች ነቢያት ተጠንቀቁ ፡፡” ማቴ.7፤15 ክፍል አምስት

የተወደዳችሁ አንባብያን!
እንደምን ሰነበታችሁ ?
ባለፈው በክፍል አራት ጽሁፋችን የካህናትን አገልግሎት በሚመለከት ጽሁፍ እንመለሳለን ባልነው መሰረት እነሆ ዛሬ እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ ካቆምንበት “‹‹የአዲሰ ኪዳን መካከለኛ» በመጽሐፍ ቅዱስ ሲመዘን ” ብለን በጀመርነው ርዕስ  እንቀጥላለን፡፡
  1.  ከመጽሐፉ ከገጽ 8 የተወሰደ ፦ ‹‹…ዛሬም በሰው ሥርዓት የተሸሙትን ምድራውያን ካህናት አልፈን በመምጣት እግዚአብሔር በሾመው ሰማያዊ ሊቀካህን እግር ሥር እንውደቅ፤ምሕረትም እናገኛለን፡፡››
  2. ከመጽሐፉ ከገጽ 12 የተወሰደ   ‹‹…በመሆኑም በወንጌል ቃል ለተገለጠው እውነት ታማኝ ሊሆኑ ባልቻሉት በዘመናችን አሮኖችና ኤሊዎች መገልገልን ትተን በሰማያዊት መቅደስ እግዚአብሔር ወዳስቀመጠልን ወደታመነው ሊቀካህናት ወደ ኢየሱስ ዘንድ ልንኮበልል ያሰፈልጋል፡፡››
  3. ከመጽሐፉ ከገጽ 17 የተወሰደ ‹‹ከክርስቶስ ወደ ሐዋርያት ከሐዋርያት ወደ ተከታዮቻቸው እየተባለ ሲወርድ ሲዋረድ እስከ ዘመናችን የደረሰ የተለየ የክህነት መስመር የለም፡፡››
በማለት ለጻፉት ክህደታቸው ምላሽ የሚሆኑትን የሚከተሉትን የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅሶች እንመልከት

“ከሐሰተኞች ነቢያት ተጠንቀቁ ፡፡” ማቴ.7፤15 ክፍል አራት

ከቁጥር ሦስት የቀጠለ
የተወደዳችሁ አንባብያን!
እንደምን ሰነበታችሁ ?
ባለፈው በክፍል ሦስት ጽሁፋችን ‹‹እኔ  መንገድና  እውነት ሕይወትም ነኝ...›› በሚለው ርዕስ እንመለሳለን ባልነው መሰረት እነሆ ዛሬ እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ ካቆምንበት “‹‹የአዲሰ ኪዳን መካከለኛ» በመጽሐፍ ቅዱስ ሲመዘን ” ብለን በጀመርነው ርዕስ  እንቀጥላለን፡፡ 

1/ከመጽሐፉ ከገጽ 8 የተወሰደ ፦
‹‹አነ ውእቱ ፍኖትኒ ወጽድቅኒ ወሕይወትኒ አልቦ ዘይመጽእ ኀበ አብ ዘእንበለ እንተ ኀቤየ ›› ማለትም ‹‹እኔ መንገድና እውነት ሕይወትም ነኝ በእኔ በቀር ወደ አብ የሚመጣ የለም ››በማለቱ በእርሱ መንገድነት ካልሆነ በቀር በሌሎች  መንገዶች ወደ እግዚአብሔር መቅረብ የማይቻል መሆኑን አረጋግጧል/ዮሐ.14፤6 እዚህ ላይ ኢየሱስ ክርስቶስ ራሱን ‹‹መንገድ›› ብሎ ጠርቷል፤መንገድ በመንገደኛውና መንገደኛው በሚደርስበት ቦታ መካከል የተዘረጋ እንደሆነ ሁሉ ክርስቶስም ሰማያዊ መንገደኞች በሆንነው በእኛና በእግዚአብሔር መካከል ያለ መካከለኛ ነው፡፡ ከእርሱም በቀር ሌላ መካከለኛ የለም፡፡›› በማለት ጽፈዋል፡፡
ከዚህ በላይ ያስነበብናችሁ ከመጽሐፋቸው ቃል በቃል የተወሰደ ሲሆን ሃሳቡን ጠቅለል በማድረግ በሁለት ከፍለን እናየዋለን፡፡ ይኸውም ፦
     ሀ/ ሐሰታቸውን እውነት ለማስመሰል የተጠቀሙበትን የግዕዙን ጥቅስ ከትክክለኛው መጽሐፍ ቅዱስ አምጥተን፤ 
     ለ /‹‹መንገድ›› የሚለው ቃል በመጽሐፍ ቅዱስ ያለውን ትርጉም የተወሰኑ ጥቅሶችን መሰረት አድርገን  እንመለከተዋለን፡፡

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በነገር ሁሉ ማስተዋሉን ይስጠን፡፡

Sunday, January 25, 2015

“ከሐሰተኞች ነቢያት ተጠንቀቁ ፡፡” ማቴ.7፤15 ክፍል ሦስት

ከቁጥር ሁለት የቀጠለ
የተወደዳችሁ አንባብያን!
     ቀደም ብለን ባስነበብናችሁ ሁለት ክፍሎች የቤተ ክርስቲያን ሳይሆኑ በተለያየ መንገድ የቤተ ክርስቲያን መስለው ስለሚያሳስቱ መናፍቃን የተወሰነ ግንዛቤ ለማሰጨበጥ ሞክረናል፡፡ሆኖም ዋና ዋናውን ጥፋታቸውን ለማመላከት ያህል ነው እንጂ የማሳሳቻ ስልታቸው ይህ ብቻ ነው ማለት አይደለም ፡፡ከሚናገሩትና ከሚጽፉት በተጨማሪ ዲያቆን ፣ካህን፣መነኩሴ፣ሰባኬ ወንጌል፣ወ...መስለው ለማሳሳት ካባውን፣ቆቡን፣መስቀሉንና ቀሚሱን ለብሰው ከበሮውን፣ ጸናጽሉን፣መቋሚያውንና የመሳሰለውን የቤ/ ንዋያተ ቅድሳት ይዘው በተለያዩ የሕዝብ መገናኛዎች ሳይቀር /የቴሌቪዥን ጣቢያዎች ጨምሮ/ የሐሰት ትምህርታቸውን በቤተ ክርስቲያናችን ስም ያስተላልፋሉ፡፡እኛ የተዋህዶ ልጆች የእኛና የእነሱ የሆነውን ለመለየት ነቅተንና ተግተን እራሳችንንም ሆነ ቤተ ክርስቲያናችንን ከስህተቱ መጠበቅ ይኖርብናል፡፡

ከፍሬያቸው ታውቋቸዋላቸሁ

     ከላይ በመግቢያችን ላይ በጠቀስነው ወንጌል በጎችንና ተኩላዎችን መለየት የሚንችለው በሚሰሩት ሥራ እንደሆነ ተመልክተናል፡፡ከዚህ በመቀጠል ከእኩይ ሥራቸው አንዱ የሆነውንና በእነሱው ከሚዘጋጁት የተለያዩ መጽሐፎቻቸው አንዱ የሆነውንየአዲሰ ኪዳን መካከለኛየተባለውን መጽሐፋቸውን እኛ ደግሞ “‹‹የአዲሰ ኪዳን መካከለኛ» በመጽሐፍ ቅዱስ ሲመዘን በሚል ርዕስ እናየዋለን፡፡

Monday, January 19, 2015

“ ከሐሰተኞች ነቢያት ተጠንቀቁ ፡፡” ማቴ.7፤15“ ክፍል ሁለት

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን፡፡

ከቁጥር አንድ የቀጠለ
ተከበራችሁ አንባብያን!
     “ ከሐሰተኞች ነቢያት ተጠንቀቁ ፡፡”በሚለው ርዕስ እንደ መግቢያ የሆነውን ክፍል አንድን ተመልክተን በይቀጥላል አቆይተነው እንደነበር የታወሳል፡፡ ስለሆነም በገባነው ቃል መሰረት ወደ ዝርዝር ጉዳዩ ከመግባታችን በፊት ነገር ከሥሩ ውሃ ከጥሩ ነውና በአሁኑ ጊዜ እራሳቸውን  “ተሐድሶ ዘኦርቶዶክስ ተዋህዶ” ብለው ስለሚጠሩት ክፍሎች  ወቅታዊ ግንዛቤ መጨበጥ ይኖሮብናል፡፡
     እነዚህ ክፍሎች ቀደም ባሉት በ1980ዎቹ ዓመታት እንዲህ እንደ አሁኑ ሳይደራጁ ማለትም ገና በጽዋ ማህበር ደረጃ ይሰባሰቡ በነበረ ጊዜ ቤተ ክርስቲያንን የማፍረስ ዓላማቸውን እንዲህ በለው ገልጸውት ነበር፡፡“ አስቀድሞ የተመሠረተው መሠረት (የኦርቶዶክስ ተዋህዶ ሃይማኖት) በአንድ ጊዜና በቀላሉ ተገርስሶ ሊወድቅ አይችልም፡፡እኛ ሥርዓቱን ለይምሰል እየፈጸምን ውስጥ ውስጡን የእኛን እውነት ስናስተምር ያ የቀድሞው መሰረት ቀስ በቀስ እየተሸረሸረ ሲወድቅ ያን ጊዜ የኛ መሰረት በዚያ ላይ ይመሰረታል፡፡”በማለት ነበር ገና ከጅምሩ ከሐዋርያው ከቅዱስ ጳውሎስ መልእክት ጋር የተጣሉት፡፡ እንጠቅሳለን ፦“በሐዋርያትና በነቢያት መሠረት ላይ ታንጻችኋል የማዕዘኑም ራስ ድንጋይ ክርስቶስ ኢየሱስ ነው፡፡ኤፌ.2፤20-21 እንዲሁም“ ከተመሰረተው በቀር ማንም ሌላ መሠረት ሊመሰርት አይችልምና ፤እርሱም ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡” 2ኛ ቆሮ.3፤11 
  ቅ/ጳውሎስም ይህንን መልእክት የጻፈው ከራሱ ልብ አመንጭቶ ሳይሆን የዓለም መድኃኒት ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተናገረውንና ወንጌላዊው ማቴዎስ በወንጌሉ ምዕ.16 ቁ.16-20 እንዲህ ብሎ የመዘገበውን መሠረት አድርጎ ነው፡፡ “ስምዖን ጴጥሮስም መልሶ አንተ ክርስቶስ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ነህ ” አለ፡፡ጌታችንም መልሶ…“.በዚችም ዓለት ላይ ቤተ ክርስቲያኔን እሰራለሁ፤ የገሃነም ደጆችም አይችሉአትም፡፡…” በማለት

Tuesday, January 13, 2015

“ ከሐሰተኞች ነቢያት ተጠንቀቁ ፡፡” ማቴ.7፤15“ ክፍል አንድ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን::

    “የበግ ለምድ ለብሰው ከሚመጡባችሁ በውስጣቸው ግን ነጣቂዎች ተኩላዎች ከሆኑ ከሐሰተኞች ነቢያት ተጠንቀቁ ፡፡ ከፍሬያቸው ታውቋቸዋላችሁ፡፡ ከእሾህ ውይን ክኩርንችትስ በለስ ይለቀማልን ? እንዲሁ መልካም ዛፍ ሁሉ መልካም ፍሬ ያደርጋል፡፡ክፉም ዛፍ ክፉ ፍሬ ያደርጋል፡፡ማቴ.715-18           
      ይህንን ኃይለ ቃል የተናገረው ጌታችን አምላካችንና መድሐኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ በዚህ ክፍለ ትምህርት ጌታችን ተጠበቁ ፣ተጠንቀቁ ብሎ ያስተማረን  እውነተኞቹን በጎች መስለው በበጎቹ መንጋ ውስጥ የተቀላቀሉትን ተኩላዎች መለየት እንድንችል ሲሆን የማንነታቸው መለያው የስራ ፍሬያቸው እንደሆነ ገልጾልናል፡፡ስለዚህ የሰውን ልቡና መርምሮ የሚያውቀው ልዑል እግዚአብሔር ብቻ ሲሆን እኛ ግን ማንንም ሰው የሚናገረውንና የሚሰራውን አይተንና ሰምተን ምንነቱን ማወቅ እንችላለን ማለት ነው፡፡ስለሆነም በዚህ ሐሰት በነገሰበት፤እውነትና እውነተኛ በጠፋበት አሰጨናቂ ዘመን መናፍቁን ከእውነተኛው አማኝ ለይተን እራሳችንንና ሌላውንም ከክህደትና ከኑፋቄ መጠበቅ ፤ከአባቶቻችን የተረከብናትን በነቢያትና በሐዋርያት መሠረት ላይ የታነጸችውን ቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ተዋህዶ ሃይማኖታችን እምነቷ፣ሥርዓቷና ትውፊቷ ሳይፋለስ ለቀጣዩ ትውልድ እንድትተላለፍ ማድረግ የሁላችንም መንፈሳዊ ግዴታ ስለሆነ ከማንኛውም ጊዜ በላይ በሃይማኖትም ሆነ በምግባር ጠንክረን መገኘት ያለብን ጊዜው አሁን እንደሆን ማስተዋል ይገባናል፡፡
     ሁላችንም እንደምናየውና እንደምናውቀው በዓለማችን ውስጥ አንድ ዓይነት መጽሐፍ ቅዱስ ይዘው እንደየራሳቸው ስሜት እየተረጎሙ የየራሳቸውን የእምነት ድርጅት አቋቁመው